ደብረ ዘይት (የዐቢይ ጾም አምስተኛ ሳምንት)

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሕዱ አምላክ አሜን

በዓለ ደብረ ዘይት

ትርጉሙ፦ ደበረ ዘይት ትርጉሙ የወራ መብቀያ፣ በወይራ ደን የተሸፈነ ተራራ ማለት ነው። ወይም «ደብር» ማለት «ተራራ» ማለት ሲሆን «ዘይት» ማለት ደግሞ «ወይራ» ማለት ነው። በተገናኝ «ደብረ ዘይት» ማለት የወይራ ዛፍ የሞላበት፣ የበዛበት፣ የይወራ ተራራ ማለት ይሆናል።

ከኢየሩሳሌም በስተምሥራቅ የሚገኝ ቦታ የሚገኝ ተራራ ሲሆን በመካከል የቄድሮን ሸለቆ ብቻ ነው ያለው። ከግርጌው ጌቴ ሴማኒ የተባለው የአትክልት ስፍራ ይገኛል። የጸሎተ ሐሙስ ማታ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተያዘበትና በኋላም የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቅዱስ ሥጋዋ ያረፈበት ወይም የድንግል መካነ መቃብር በዚህ ተራራ ግርጌ ይገኛል። ቤተ ፋጌ እና ቢታንያ በኮረብታው ጫፍ እና በምስራቅ ዳገታ ላይ ይገኛሉ። ይህ ተራራ በመፅሐፍ ቅዱስ የሚገኙ ብዙ ድርጊቶች የተደረጉበት ቦታ ነው። ጌታችን ስለ ቤተ መቅደሱ መፍረስ፣ ስለ ዓለም ፍጻሜና ስለ ዳግም ምጽአት በዚህ ተራራ ላይ በትንቢት መልክ ተናገረ (ማቴ.24፥3)። በዚሁ ተራራ ላይ ወደ ሰማይ ዐረገ (ሉቃ. 24፥50)። በዚሁ ተራራ ላይ ቀን በከታማና በገጠር ሲያስተምር ውሎ ሌሊት የሚያድርበት የኤሌዎን ዋሻ ይገኛል። በኋለኛው ምጽ አቱ በዚሁ ቦታ እንደሚገለጥ ትንቢት ተነግሯል።(ዘካ. 14፥3–5)።

ስያሜው፦ የዓቢይ ጾም እኩሌታ ላይ ያለው ሰንበት በዚህ ተራራ ተጠርቷል። ይህንን ዕለት የቤተ ክርስቲያናችን ሊቅ ቅዱስ ያሬድ የዳግም ምጽአት አድርጎ መዝሙሩን ጽፏል። በዚህ ተራራ ላይ «እርሱም በደብረ ዘይት ተቀምጦ ሳለ፥ ደቀ መዛሙርቱ ለብቻቸው ወደ እርሱ ቀርበው፦ ንገረን፥ ይህ መቼ ይሆናል? የመምጣትህና የዓለም መጨረሻ ምልክቱስ ምንድር ነው? አሉት» (ማቴ.24፥3)። ተብሎ እንደተጻፈው ለደቀ መዛሙርቱ የደግም ምጻቱን፣ የዓለምን ፈጻሜ፣ የትንሣኤ ሙታንን፣ ትምህርት በሰፊው ስላስተማረ በዓሉ በተራራው ስም ተሰይሟል።

የደቀ መዛሙርቱ ጥያቄ

ከዕለታት አንድ ቀን ደቀ መዛሙርቱ የቤተ መቅደሱን ሥነ ሕንፃ በትኩረት እያንዳንዱን ነገር በመመልከት አደነቁ። ጧት በጸሎት ጊዜ ጸሎታቸውን አድረሰው ሲጨርሱ የጧት ፀሐይ አርፎበት ያሸበረቀውን ቤተ መቅደስ ውበቱን አስተውለው ምን ጥበበኛ እንዳሠራው እየተነጋገሩ ጌታችንንም አብሮ እንዲያደንቅ ሲጠብቁ አስደንጋጭ ነገር ተናጋረ። ያ የሚያደንቁት ቤተ መቅደሱ እንደሚፈርስ፤ አያይዞም ከሞት በኋላ ተነሥቶ እንደሚያረግና ነገር ግን ዓለምን ለማሳለፍ ዳግም እንደሚመጣ ወደፊት የሚሆኑ ሚሥጢራትን እና በቤተ መቅደሱና በሕዝቡ ላይ ሊደርስ ያለውን በትነሹ ጥቆመቸው። ይህም ነገር እረፍት ነሳቸውና ወደ ደብረ ዘይት ከተሻገሩ በኋላ በሰፊው እንዲገልጽላቸው ጠየቁት። ጥያቄውም «እርሱም በደብረ ዘይት ተቀምጦ ሳለ፥ ደቀ መዛሙርቱ ለብቻቸው ወደ እርሱ ቀርበው፦ ንገረን፥ ይህ መቼ ይሆናል? የመምጣትህና የዓለም መጨረሻ ምልክቱስ ምንድር ነው? አሉት» (ማቴ.24፥3) የሚል ነው። በዚህ የጥያቄያቸው ክፍል እንደምናየው ጥያቄያቸው ዕለትና ምልክት ነው። ወይም «መቼ» እና «ምን» የሚል ነው። የቤተ መቅደሱ መፍረስ መቼ ይሆናል? የዓለም መጨረሻና የመምጣትህስ ምልክቱ ምንድን ነው? ጌታችንም በቀኙ ያቁመንና ወደ ግራም ወደ ቀኝም ሳይል በጥያቄያቸው ላይ ብቻ አተኩሮ ሰፊ መልስ ሰጥቷቸዋል።

መቼ ይሆናል ላሉት የመጀመሪያው ጥያቄ «ስለዚያች ቀንና ስለዚያች ሰዓት ግን ከአባት ብቻ በቀር የሰማይ መላእክትም ቢሆኑ ልጅም [ሰውም] ቢሆን የሚያውቅ የለም» (ማቴ.24፥.36)። ሲል አጭር መልስ ሲሰጥ።ስለ ሁለተኛው ጥያቄ ስለ ምልክት ጉዳይ ግን መሸከም እስኪያቅታቸው ድረስ አስተምሯቸዋል። በመልሱም ውስጥ ማስጠንቀቂያዎች፣ ምክሮች፣ ማጽናኛዎችና ምሳሌዎች በብዛት ቀርበዋል በተደጋጋሚ ተወስተዋል።

ምልክቶቹ

1/ ሐሰተኞች ክርስቶሶች

ጌታችን በአንደኛ ደረጃ የተናገረው ምልክት በተለያየ ጊዜ በተለያየ ሀገር ብዙ ሐሰተኞች ክርስቶሶች እንደሚነሡ ነው። የጌታ ቃል አይቀርምና ከዚህ ቀደም ብዙ ሰዎች እኔ ክርስቶስ ነኝ እያሉ ተነሥተው ነበር። ዋናው በዮሐንስ ራእይ ዕራፍ 13 አውሬ ተብሎ የተጠቀሰውና በቅዱስ ጳውሎስ «የዐመፅ ሰው እርሱም የየጥፋት ልጅ» የተባለው ብዙ ጥፋትና መከራ የሚያደርሰው እና በለ 666 መለያ ምልክቱ ሐሳተኛ ክርስቶስ እሲከገለጥ ደረስ መንገድ ጥራጊዎች የሆኑ አለማማጅ ሐሰተኞች ክርስቶሶች ተነሥተዋል። በእውነተኛው ንጉሥ ክርስቶስ ዳግም መምጣት የሚደመሰሰው ሐሳዊ መሲሕ የመጨረሻውና ለሦስት ዓመት ከመንፈቅ ቤተ ክርስቲያንን የሚወጋ የታላቁ መከራ ፈጻሚና አስፈጻሚ ይሆናል። ለዚህ ነው መድኃኒታችን እስኪመጣ ድረስ እናዳንሰናከል አስቀድሞ «ብዙዎች፦ እኔ ክርስቶስ ነኝ እያሉ በስሜ ይመጣሉና፤ ብዙዎችንም ያስታሉ … በዚያን ጊዜ ማንም፦ እነሆ፥ ክርስቶስ ከዚህ አለ ወይም፦ ከዚያ አለ ቢላችሁ አትመኑ» (ቁጥ. 5 እና 23) ሲል ያስጠነቀቀን።

በሀገራችንም በኢትዮጵያ በአፄ ልብነ ድንግል ዘመነ መንገሥት እኔ ክርስቶስ ነኝ የሚል ሐሳዊ/ሐሰተኛ ክርስቶስ ተነሥቶ እንደነበር በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ተመዝግቧል። ይህ በሀገራችን ተንሥቶ የነበረው ሐሳዊ ክርስቶስ ልክ እንደ እውነተኛው ክርስቶስ 12 ሐዋርያት፣ 72 አርድእትና 36 ቅዱሳት አንስት አስከትሎ እኔ ክርስቶስ ነኝ እያለ ሲንቀሳቀስ ንጉሡ አስቀርበው አንተ ማን ነህ? ቢሉት በድፍረት እኔ ክርስቶስ ነኝ አላቸው። ንጉሡም ክርስቶስማ ከደንግል ማርያም ተወልዶ አስተምሮ፣ ተሰቅሎ፣ ዓለምን አድኖ ከሞት ተንሥቶ ዐርጓል ዳግም ዓለምን ለማሳለፍ ይመጣል አንተ ግን ማነህ? ቢሉት አዎ ትክክል ነው። ከዚህ ቀደም ከቤተ እሥራኤል ከምትሆን ከድንግል ማርያም ተወልጀ፣ አስተምሬ ተሰቅየ ሙቼ ተነሥቼ ዐርጌ ነበር፤ አሁን ድግሞ ጥቁሮች አፍርካውያን ባይታወር አደረገን እንዳይሉኝ ከእናቴ ከድንግል መርዐተ ወንጌል ለጥቁሮቹ ዳግም ተወልጀ ነው አላቸው። ንጉሡም ሰይጣን በሰው እያደረ እንዴት ይጫወታል ብለው በሰይፍ አስቀጡት ተካታዮቹም ተበተኑ ይባላል።

2/ ጦርነት

ጦርነት ዱሮም ነበረ። የዚህ ዘመን ጦርነት ግን የበዛና በብዙ ሀገራት የሚካሄድ ነው፣ የዱሮ ጦርነት ሴቶችን፣ አቅመ ደካማ ሺማግሌዎችንና ሕፃናትን ለእልቂት የማያጋልጥ ነበር። የዘመናችን ጦርነት ግን ማንንም የማይለይ ለማንም የማይራራ ሁሉን የሚደፈጥጥ የሁሉን ደም የሚያፈስ አስቃቂነቱ ከመግለጫ ቋንቋ በላይ ሆኖ ይታያል። ይህንንምም ጌታችን የዳግም ምጽ አቱን ምልክት ለጠየቁት ለደቀ መዛሙርቱ ሁለተኛ ምልክት አድርጎ «ጦርንም የጦርንም ወሬ ትሰሙ ዘንድ አላችሁ፤ ይህ ሊሆን ግድ ነውና ተጠበቁ፥ አትደንግጡ፤ ዳሩ ግን መጨረሻው ገና ነው። ሕዝብ በሕዝብ ላይ መንግሥትም በመንግሥት ላይ ይነሣልና» (ቁጥማቴ .6-7) ሲል ተናግሮታል።

3/ ረሀብ

የረሀብ ወሬ ወደ ሌላ ሀገር መሄድ ሳያስፈልገን በገዛ ሀገራችን የምናየው የምንዳሳሰው ያለው ለመርዳት የሌለው ለጸሎት የሚሮጥባት ሀገራችን ኢትዮጵያ አለች። ይህም ሰው ሰራሽ ችግር ለጠላቶቻችን ማሣለቂያ አድርጎን ይኖራል። በተለው የተፈጥሮ ችግር ሳያጋጥማት በሰው ሰራሽ ችግር 8 000 000 ሕዝብ ለአስቸኳ ምግብ ርዳታ የተጋለጠበት ሁኔታ ያሳዝናል። ይህም ዓይነት በጥልና በተንኮል በጭካኔ ሰዎች የሚፈጥሩት ችግር የምጽአት ሦስተኛ ምልክት ሆኖ በጌታችን ለደቀ መዛሙርት ተነግሯል «ረሀብም ቸነፈርም በልዩ ልዩ ሥፍራ ይሆናል» (ማቴ. 24፥7) ተብሎ እንደተጻፈ።

4/ የምድር መንቀጥቀጥ

የመሬት መንቀጥቀጥ ባለፉት ዓመታት በርካታ ጉዳት በተለያዩ ሀገሮች እንዳደረሰ የሚዘንጋ አይደለም። በ1999፣ ጀምሮ እስከ ዛሬ በተለያዩ ሀገሮች በተለያየ ጊዜ የበዙዎችን ሕይወት የቀጠፈ አያሌዎችን ቤት ንብረት አልባ ያደረገ የመሬት መቀጥቀጥ ተከሥቷል። በሄይቲ፣ በታይዋን፣ በቱርክ፣ በፊልፕንስ፣ ወዘተ ተከሥቷል። ይህም ለደቀ መዛሙርቱ የዓለም ፍጻሜ ምልክት የማግኘት ጥያቄ የተሰጠው «የምድርም መናወጥ በልዩ ልዩ ስፍራ ይሆናል» (ማቴ. 24፥7) ተብሎ በጌታ የዓለም ፍጻሜ ምልክት ተደርጎ የተነገረው ቃል አይቀርምና እየሆነ ነው።

5ኛ/ የክርስቲያኖች መከራ

የክርስቲያኖች መከራ እየጀመረ ይመስላል። ሰይጣን ኢቴስቶችን፣ እስላሞችንና አይሁድን በመጠቀም በክርስቲያኖች ላይ ከምን ጊዜውም በላይ ችግር መፍጠር የቸመረበት ጊዜ ነው። በአውሮፓ የክርስቲያኖች ጥያቄ ቶሎ የማይመልስ የቤተ ክርስቲያንን ጥያቄ ለማስተናገድም መንግስታዊ መሥሪያ ቤቶች ፈቃደኛነታችውን እያጡና ይህንን ወንጀላቸውን ለመሸፈንም በሕግ አንቀጽ እየፈጠሩለት ይታያሉ። «በዚያን ጊዜ ለመከራ አሳልፈው ይሰጡአችኋል ይገድሉአችሁማል፥ ስለ ስሜም በአሕዛብ ሁሉ የተጠላችሁ ትሆናላችሁ» (ማቴ. 24 ቁጥ.9)። ተብሎ እንደተጻፈው ሃይማኖተኛነት እንደ ኋላ ቀርነት ከሐዲነት እንደተራማጂነትና ሥልጡንነት የሚታይበት ዘመን ላይ እንዳለን ግልጽ ነው። ይህ በአጭር ጊዜ ውስጥ አመለካከት ክርስቲያኖችን ወደ ማግለልና ወደ መወንጀል የሚያድግ መሆኑ ከሚታዩት ፍንጮች መረዳት ይቻላል።

በእንዲህ አይነት የመከራ ዘመን የክርስቶስ ተቃዋሚዎች በክርስቲያኖች ላይ ከሚያመጡት መከራ የበለጠ የክርስቲያኖች እርስ በእርስ መከዳዳት ጭንቁን ያከፋዋል መከራውን መራራ ያደርገዋል «በዚያን ጊዜም ብዙዎች ይሰናከላሉ እርስ በርሳቸውም አሳልፈው ይሰጣጣሉ እርስ በርሳቸውም ይጣላሉ» (ማቴ.24፥10) ተብሎ በጌታ እንደተነገረ ከሐድያኑ ሆነ ብለው በእቅድ በክርስቲያኖች መካከል መከዳዳትን በመፍጠር ለዚህ ነው ክርስቲአኖች ክርስትናን መተው ያለባቸው ፍቅርና መተማመንን ሰላምና ጸጥታን ለማሰፈን ነው ክርስትናን የምንቃወመው እያሉ ድጋፍ ያሰባስባሉ።

6/ ሐሰተኞች ነቢያት

በዲያብሎስ መንፈስ ምትሐታዊ አሠራርን እያሳዩ አይቻላቸው እንጂ ቢቻላቸው የተመረጡትን ሳይቀር የሚያስቱ ነቢያት ነን የሚሉ ብዙዎች ደፋሮች እንዲመነሡ ጌታችን ስድስተኛ የዳግም ምጽአቱ ምልክት አድርጎ ጠቅሷቸዋል። በአሁኑ ዘመን በሀገራችንም ነቢያት ነን የሚሉ አጭበርባሪዎች እንደ አሸን ፍልተዋል።

እነዚምህም በነቢያ ኤልያስ፣ በነቢዩ ኤልሣዕ ስም እያጭበረበሩና እየዋሹ በምትሐታዊ አሠርራር የሚያስቱ ሐሰተኞች እንደሚነሱ ሌላው የዳግም ምጽአቱ ምልክት ሆኖ «ብዙ ሐሰተኞች ነቢያትም ይነሣሉ ብዙዎችንም ያስታሉ …ሐሰተኞች ክርስቶሶችና ሐሰተኞች ነቢያት ይነሣሉና፥ ቢቻላቸውስ የተመረጡትን እንኳ እስኪያስቱ ድረስ ታላላቅ ምልክትና ድንቅ ያሳያሉ … እንግዲህ፦ እነሆ፥ በበረሀ ነው ቢሉአችሁ፥ አትውጡ፤ እነሆ፥ በእልፍኝ ነው ቢሉአችሁ፥ አትመኑ፤ » (ማቴ 24 ቁጥ.11፥ 24 እና 26) ተብሎ በጥብቅ ተነግሯል። እንግዲህ በዘመናችን በሀገራችን ሆነ በሌላው ዓለም በነቢይነትና በሰባኪነት ስም የሚደረገውን የንግድና የርኩሰት እንቅስቃሴ በማስተዋል መከታተልና መጠበቅ ያስፈልጋል።

7/ የፍቅር ማጥፋት

ሌላውና አሳዛኙ ጉዳይ የፍቅር መቀዝቀዝ ነው። ፍቅር የሕግ ፍጻሜ ነው። የሰው ልጅ ፍቅርን ማጥፋት እና ማጣት የሌለበት ሀብቱ ነው። አሁንም «ከዓመፃም ብዛት የተነሣ የብዙ ሰዎች ፍቅር ትቀዘቅዛለች» (ማቴ.24፥12) የሚለው ትንቢት እንዳይፈጸምብን ፍቅርን መንከባከብ፣ ማልማትና ማስፈት ይገባል። ፍቅር የመንፈስ ቅዱስ ፍሬ ነው። ፍቅር የመልካምና በጎ ንገር ሁሉ መገኛና ምንጭ ነው።

8/ የወንጌል መዳረስ

የወንጌል ለዓለም መዳረስ ለደቀ መዛሙርቱ የዳግም ምጽአቱ ምልክቶች ሁነው ከተሰጡት አንዱ ነው። በፍርዳ ቀን በመጫረሻው ጊዜ በክርስቶስ አምኖ እና እምነቱን በሥራ ግልጾ ስለመኖር ሲጠየቅ አልሰማሁም አላየሁም አላወኩም የሚል አያመልጥም «ለአሕዛብም ሁሉ ምስክር እንዲሆን ይህ የመንግሥት ወንጌል በዓለም ሁሉ ይሰበካል፥ በዚያን ጊዜም መጨረሻው ይመጣል» (ማቴ. 24፥ 14) ተብሎ እንደተነገረው በሁሉም ቤት ወንጌል ይሰበካል ከሁሉም ዘንድ ይገኛል።

የምጽአቱ ምሳሌዎች

ፍጥነቱ፦ ፈጥነቱ እንደ መብረቅ ነው። «መብረቅ ከምሥራቅ ወጥቶ እስከ ምዕራብ እንደሚታይ፥ የሰው ልጅ መምጣት እንዲሁ ይሆናል» (ማቴ 24፥ 27):: ተብሏልና።

ቀኑ አለመታዎቁ፦ እንደ ሌባ ነው። ያን ግን እወቁ፤ ባለቤት ከሌሊቱ በየትኛው ክፍል ሌባ እንዲሚመጣ ቢያውቅ ኖሮ፥ በነቃ ቤቱም ሊቈፈር ባልተወም ነበር … የሰው ልጅም በማታስቡበት ሰዓት ይመጣል (ቁጥ. 43-44)።

ለታሪካዊ ማስገንዘቢያ የኖህ ዘመንም እንደዚሁ ባልታሰበ ሠዓት እንደሚመጣ ማስገንዚያ ሆኖ በጌታችን ቀርቧል። (ከቁጥ. 37-39)።

ወቅታዊ መልእክቱ

ተጠንቀቁ፦ ማንም እንዳያስታችሁ ተጠንቀቁ (ቁጥ.4)።

ንቁ፦ጌታችሁ በምን ሠዓት እንዲመጣ አታውቁምና እንግዲህ ንቁ (ቁጥ. 42)

ተማሩ እወቁ፦ እንዲሁ እናንተ ደግሞ ይህን ሁሉ [ከላይ የተናገራቸውን ምልክቶች ሁሉ] ስታዩ በደጅ እንደ ቀረበ እወቁ (ቁጥ. 33)።

አትደንግጡ፦ ይህ ሊሆን ግድ ነውና ተጠበቁ፥ አትደንግጡ (6)

ትጉና ጸልዩ፦ ነገር ግን ሽሽታችሁ በክረምት ወይም በሰንበት እንዳይሆን ጸልዩ (20)

ተዘጋጅታችሁ ኑሩ፦ ስለዚህ እናንተ ደግሞ ተዘጋጅታችሁ ኑሩ፥ የሰው ልጅ በማታስቡበት ሰዓት ይመጣልና።(44)።

ጽኑ፦ እስከ መጨረሻ የሚጸና ግን እርሱ ይድናል (ቁጥ.13)።

እነዚህን ሁሉ ምክሮች፣ ማስጠንቀቂያዎችና ማፅናኛዎች በአእምሮ ጽላት ቀርፆ በማስተዋል በሃይማኖት እና በክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር ጸንቶ የኖረ የሕይወትን ቃል ሰምቶ የክብር፣የድልና የጽድቅ አክሊልን ተሸልሞ በዘላለማዊ ደስታ ይኖራል።

ሦስተኛ የሰው ዘር የጋራ ልደት እና ዕድገት

ከዚህ ሁሉ በኋላ በእግዚአብሔር ዘንድ ቀነ ቀጠሮ የተያዘላት ዓለም ወደ ፍጻሜዋ ታመራለች፣ ጣዕሟ፣ ለዛዋ ሁሉ ይሟጠጣል፣ ፍጻሜ ዓለም ይሆናል፡፡ ምድር ከመሠረቷ ትናጋለች፣ ፀሐይ ትጨልማለች፣ ከዋክብትም እንደ ቃርያ ፍሬ ከሰማይ ይረግፋሉ፡፡ (መዝ. 12፥ 2፤ ኢሳ. 13፥ 6-13፤ ኢዩ. 2፥ 10-11፣ 30-32፤ ማቴ. 24፥ 29-41፤ ራዕይ 6፥12-17)፡፡

በታላላቅ ድንጋዮች የታተሙ መቃብሮች በውስጣቸው የያዙአቸውን ሙታን ይሰጣሉ፣ የሙታን ሥጋ ከረጅም የእንቅልፍ ዓለም ይባንንና ሁሉም በአንድ ቀን ከመቃብር ተወልደው በአንድ ቀን አድገው ወደ ፍርድ አደባባይ ይሰበሰባሉ፣ ታላቁ ዘንዶ ለብዙዎች ስሕተት ምክንያት የሆነው ዲያብሎስ ከነሠራዊቱ ለዘላለም በማይፈታ በእሳት ሰንሰለት ታስሮ ወደ ገሃነመ እሳት ይጣላል፡፡ ፊተኞቹ ሰማይና ምድር ከፍጡራን ፊት እንደወረቀት ተጠቅልለው ያልፋሉ፣ ስፍራም አይገኝላቸውም ለዘለአለምም ያልፋሉ፡፡ (ኢሳ. 13፥ 6-13፤ መክ. 12፥ 17፤ 1ኛ ተሰ. 4፥ 13-18፤ 2ኛ ጴጥ. 3፥ 10)፡፡

በበጉ ደም የተዋጁና ሃይማኖታቸውን የጠበቁ ታማኝ የክርስቶስ ልጆች ገናናውንና ታላቁን አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስን ሊቀበሉ በታላቅ ክብር በደመና ወደ ሰማይ ይነጠቃሉ፡፡ የአብ ልጅ የድንግል ማርያም ልጅ የባሕርይ አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስም በታላቅና እጅግ አስፈሪ በሆነ መለኮታዊ ግርማ የብዙ ብዙ በሚሆኑ እልፍ አእላፋት ቅዱሳን መላእክት ታጅቦ ይመጣል፡፡ (ዘካ. 14፥ 6፤ ማቴ. 25፥ 31፤ 1ኛ ተሰ. 4፥ 16)፡፡

በዚያን ጊዜ በፊቱ ችሎ የሚቆም ማን ይሆን? (ኢዩ. 2፥ 11) አመጣጡም እንደቀደመው ከሐና ወደ ቀያፋ ከዚያም ወደ ጲላጦስ አደባባይ እያንገላቱ ሲወስዱት ዝም እንዳለ በዚህ ዓይነት አመጣጥ አይደለም፡፡ የሚመጣው በሚያስፈራና በሚያስደነግጥ መለኮታዊ ግርማና ክብር ነው፡፡ (መዝ. 49፥ 2)፡፡ መጥቶም ዝም አይልም እሳት በፊቱ ይነዳል ኃጥአንን ከፊቱ ጠራርጎ ወደ ገሃነመ እሳት የሚጨምር ጥቅል አውሎ ነፋስም አለ፡፡ (ማቴ. 24፥ 30፤ ራዕይ 1፥ 7)።

እረኛ በጎቹን ከፍየሎቹ እንደሚለይ ጻድቃንን በቀኙ ኃጥአንን በግራው ለይቶ ያቆማቸዋል፡፡ በቀኙ ያሉትን “እናንተ የአባቴ ቡሩካን ወደ እኔ ኑ ወደ አባታችሁ መንግስተ ሰማያት ግቡ፡፡” ብሎ ለዘለዓለም ሕይወት ይጠራቸዋል፡፡ በግራው ያሉትን ደግሞ እጅግ በሚያስፈራና በሚያስደነግጥ የቁጣ ቃል “እናን ርጉማን ለሰይጣንና ለመላእክቱ ወደ ተዘጋጀው ወደ ዘላለም እሳት ከእኔ ሂዱ” ይላቸዋል፡፡

ኢየሩሳሌም ሰማያዊት ለባልዋ እንደተሸለመች ሙሽራ ተዘጋጅታ ከእግዚአብሔር ዘንድ ትወርዳለች ማለት ለምእመናን ትሰጣለች፡፡ ምእመናንም ርስት መንግስተ ሰማያትን ይወርሳሉ ብርሃን ለብሰው ብርሃንን ተጎናጽፈው ለዘለዓለም በደስታ ይኖራሉ፡፡ (ማቴ. 25፥ 31-46፤ ራዕይ 21፥ 1-2)፡፡

ኦርቶዶክሳውያን! ነቢዩ ኤርምያስ “እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፡-በመንገድ ላይ ቁሙ ተመልከቱም የቀደመችውንም መንገድ ጠይቁ መልካሚቱ መንገድ ወዴት እንደሆነች እወቁ በእርስዋም ላይ ሂዱ ለነፍሳችሁም እረፍት ታገኛላችሁ” (ት.ኤር. 6፣ 16)፡፡ በማለት እንደተናገረው በቀደመችው በመልካሚቱ የሕይወትና የጽድቅ መንገድ በቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋህዶ እምነታችን እስከ መጨረሻው ድረስ ጸንተን ልንኖር ይገባል፡፡

ማጠቃለያ

ደብረ ዘይት እንግዲህ ተጽፎና ተተርጉሞ የማያልቅ ሰፊ፣ ጥልቅና ምጡቅ ትምህርትን የያዘ በዓል ነው። በደቀ መዛሙርቱ ሁለት ብቻ ጥያቄዎች ተነሥቶ ያስተማረው የዕለተ ምጽአቱ ነገር በአጭር ጽሑፍ የሚካተት ስላልሆነ በሀገር ቤት የታላቋ ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ተከታዮች ኦርቶዶክሳውያን ይህንን በዓል በየዓመቱ እንዴት እንደሚያዘክሩት በማሳየት እናቆየዋለን።

በገጠሪቱ ኢትዮጵያ ይህ በዓል በሀብታሙም በድሀውም በትልቁም በትንሹም ዘንድ በበጎ ሥራ በክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር ተከብሮና ታስቦ ይውላል። ሕዝበ ክርስቲያኑ ያለውም የሌለውም ቤት ያፈራውን ምግብ ይዞ ወደ ቤተ ክርስቲያን ይመጣና ከመንፈሳዊ አገልግሎት በኋላ አስቀድሞ ድሆችን በመጎብኘት፣ በመመገብና በማጽናናት ከደሆች የተረፈውን እርስ በእርስ በመገባበዝ፣ የተጣላ በማስታረቅ በቅፅረ ቤተ ክርስቲያን ከዋርካውና ከፅዱ ሥር አርፎ ይውላል።

ክርስቲያኑ ሕዝብ ይህንን የሚያደርግበትን ምክንያትም ሲገልጽ ዓለምን ለማሳለፍ ጌታችን የሚመጣ በዚህ ዕለት ስለሆ ሲመጣም እንዲህ ያለ ደግ ሥራ የሠሩትን ተርቤ አብልታችሁኛልና፥ ተጠምቼ አጠጥታችሁኛልና፥ እንግዳ ሆኜ ተቀብላችሁኛልና፥ ታርዤ አልብሳችሁኛልና፥ታምሜ ጠይቃችሁኛልና፥ ታስሬ ወደ እኔ መጥታችኋልና። እናንተ የአባቴ ቡሩካን፥ ኑ፤ ዓለም ከተፈጠረበት ጊዜ ጀምሮ የተዘጋጀላችሁን መንግሥት ውረሱ። ብሎ መንግሥቱን እንዲያወርሰን ነው ይላሉ።

ምእመናኑ ለምን ይህን እንደሚያደርጉ ሲጠየቁ የሚሰጡት ሁለተኛው መልስ ደግሞ የሞቱት ነፍሳት በዚህ ዕለት ይሰበሰባሉ ወይም ይመጣሉ ዘመዳቸው የሆነ ጥሬ ወይም እንጀራ ወደ ቤተ ክርስቲያን ወስዶ ለነዳያን የሰጠ እንደሆነ ደስ ይላቸዋል። የሞተ ዘመድ ያለው አንድ ሰው በደብረ ዘይት ዕለት ጥሬ ወይም እንጀራ ወደ ቤተ ክርስቲያን አምጥቶ ካልመጸወተ የዘመዱ ነፍስ መጥታ የኔስ ዘመዶች አልቀዋል ብላ አዝና ትመለሳለች ይላሉ። ምስጢሩ ከላይኛው አይርቅም።

ይህ ደብረ ዘይት ወይም አምስተኛው የዐቢይ ጾም ሰንበት ሌሎች ስያሜዎችም አሉት። በተጨማሪ ዳግም ምጽዐት፣ የፍርድ ቀን፣ የጌታ ቀን፣ ሕልቀተ/ሕልፈተ ዓለም፣ ዕለተ ፍዳ፣ ዕለተ ደይን ዳግመኛ ልደት ትንሣኤ ዘጉባዔ በመባል በመጽሐፍ ቅዱስና በቅዱስ ያረድ ድርሰቶች ይጠራል።

የእግዚአብሔር ጥሪ ሁሉም የአዳም ዘር መንግሥቱን እንዲወርሱ ቢሆንም የሰይጣንን ወጥመድና አሸከላ ሁሉ አልፈው፤ በሐሰተኞች ክርስቶሶችና በሐሰተኞች ነቢያት ምትሐታዊ ተአምራት ሳይሳቡና ሳይሰናከሉ እስከ መጨረሻው ጽንተው በዚያ በዳግመኛ ልደት እና የመጨረሻ የዋጋ ቀን በጌታቸው ቀኝ የሚቁሙ የታደሉ ናቸው።

እንግዲህ እኛን በቀኙ ያቁመን ዘንድ የአባቴ ቡሩካን ኑ ወደ ጌታችሁ ደስታ ግቡ የሚለውን የሕይወት ቃሉንም ያሰማን ዘንድ የአምላካችን የእግዚአብሔር ቅዱስ ፈቃዱ ይሁንልን።

ስለ እናቱ ቅድስት ድንግል ማርያም እመቤታችን ብሎ ልጇ መድኃኔዓለም በዚያ የሚያስፈራ ቀን ይራራልን። በዕለተ ዐርብ የፈሰሰው ክቡር ደሙ ከትንሣዔ ዘጉባዔ ክብር የሚለየንን ነውራችንን ይሸፈንልን አሜን።