ዘወረደ (የዐቢይ ጾም አንደኛ ሳምንት)

ዘወረደ(ጾመ ሕርቃን)

«ዘወረደ» ማለት «የወረደ» ማለት ነው፡፡  አምላክ ሰው ሆነ፤ ሰው አምላክ ሆነ ማለት ነው። ይህም  ጌታችን መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ  እኛን ለማዳንና ፍቅሩን ሊገልጽልን ከሰማያት መውረዱን ከድንግል ማርያም የእኛን ሥጋ መዋሐዱን የሚያዘክር፤  ከሰማየ ሰማያት ወርዶ ከቅድስት ድንግል ማርያም መወለዱን የሚያመላክት፣ የሚታወስበት፣ የሚነገርበት  የዐቢይ ጾም አንደኛው ሳምንት   ነው፡፡ዮሐ.3-13፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ለአዳም በገባዉ ቃልኪዳን መሰረት “  የዘመኑ ፍጻሜ በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር ከሴት የተወለደውን ልጁን ላከ” እንዳለ ሐዋርያዉ ቅዱስ ጳዉሎስ የጠፋዉን አዳም ፍለጋ ከአባቱ እሪና ሳይጎድል ሳይለይ ከሰማይ መዉረዱን የምናዘክርበት በዓል ነዉ።  ይህ ጾም የጾም መግቢያ የመጀመሪያ ሳምንት የምንጾመው ጾም ሲሆን ሕርቃል የሚል ስያሜ ተሰጥቶታል፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ለአዳም “ከአምስት ቀን ተኩል በኋላ ከልጅ ልጅህ ተወልጄ በመልዕልተ መስቀል ተሰቅየ አድንኃለሁ” ብሎ ለአዳም ቃል ገባለት ፡፡ ዘፍ. ፫ ፥ ፲፭  ይህ ኪዳነ አዳም ይባላል ፡፡ የቃል ኪዳን ሁሉ መሠረት ነው ፡፡ ሁለቱን ኪዳናት (ብሉይ ወሐዲስ) በፅኑዕ ተስፋ ያስተሳሰረ የረጅም ዘመናት የድኅነት ሰንሰለት ነው ፡፡ ዘወረደ እርቀ አዳም  ፤ ተስፋ አበው ፤ ትንቢተ ነቢያት ፤ ሱባኤ ካህናት መፈፀሙ ፤ ኪዳነ አዳም መሲህ መወለዱ የሚነገርበት የፍቅር አዋጅ ነው ፡፡

ዘወረደ ማለት?

  • የምስጢረ ሥጋዌ(የአምላክ ሰው መሆን) ትምህርት ነው፡፡ ዘወረደ ስንል አምላክ ወረደ ከቅድስት ድንግል ማርያም ተወለደ ፤ በፍጹም ተዋሕዶ ሰው ሆነ ማለታችን ነው ፡፡  አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሕያው ሲሆን ሞቶ በመብል ምክንያት የሞተው አዳምን  ሕያው አደረገው ፡፡ አምላክ ወልደ አምላክ በመስቀል ላይ በፈቃዱ ሞቶ ለአዳም ያለውን ታላቅ ፍቅር ገለጸ ፡፡
  • ጠላቶቹ ሳለን ከእግዚአብሔር ጋር በልጁ ሞት ከታረቅን ፥ ይልቁንም ከታረቅን በኃላ በሕይወቱ እንድናለን ፡፡ ሮሜ. 5 ፥ ፲ ፡፡ በዚህም ትህትናን ፍቅርን አስተማረን ፡፡

የመጀመሪያ የዐብይ ጾም መግቢያ እሁድ ዘወረደ ይባላል ደግሞም ጾመ ሕርቃል ይባላል፡፡ ስያሜውም፤ በ614 ዓ.ም ኪርዮስ የተባለ የፋርስ ንጉሥ ኢየሩሳሌምን በመውረር ጥቃት አደረሰ፡፡ በዚህ ወቅት በኢየሩሳሌም ንግሥት ዕሌኒ በሠራችው ቤተመቅደስ ውስጥ ሲገባ ንግሥቷ በክብር አስቀምጣው የነበረው የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል እንደ ፀሐይ ሲያበራ አገኘው፡፡ ቢነካው አቃጠለው ዲያቆናቱን አሸክሞ ሌላውን ንዋየ ቅድሳት ዘርፎ 60ሺ የሚደርሱትን አቁስሎ ገድሎ 3ሺ የሚሆኑትን ማርኮ ከተማዋንም አቃጥሎ ወደ ፋርስ ባቢሎን ይመለሳል፡፡ በዚህ ጊዜ ከጦርነቱ ያመለጡ በየዋሻው በየጉራንጉሩ ገብተው የተሸሸጉ ተሰብስበው ከ14 ዓመት በኋላ በ628 ጩኸታቸውንና የደረሰባቸውን በደል ለክርስቲየኑ የሮም ንጉሥ ሕርቃል ይነግሩታል፡፡ እርሱም ሐዋርያት ሰውን የገደለ እድሜውን በሙሉ ይጹም ስላሉ እንዴት ላድርገው አላቸው እኛ የአንተን እድሜ ተከፋፍለን እንጾማለን ብለው አንድ አንድ ሳምንት ደርሷቸው ጾሙን በሚገባ ጾመውታል፡፡ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ መስቀልና የተማረኩ ክርስቲያኖችን ለመመለስ ሕርቃል ጦር መዝዞ በኪርዮስ ላይ ተነሳበት ድል ለሕርቃል ሆነና መስቀሉን ያለበትን አጥቶ ሲቸገር መስቀሉን ሲቀብርና ዲያቆናቱን ሲያስገድል በመስኮት ሆና ያየችው ከኢየሩሳሌም የተማረከች አንዲት ብላቴና አሳይታው አውጥቶ በልብሰ መንግሥቱ ጠቅልሎ ወደ ቁስጥንጥንያ ተመለሰ፡፡ የተማረኩት በሙሉ ነጻ ወጡ ይህን ለማሰብ ለማስታወስ በተጨማሪ በኃጢአት ላይ ድል እንድናገኝ መንፈሳዊ ጦር በውስጣችን እንዲበዛልን መስቀልህ ከምርኮ እንደተመለሰ እኛንም ከኃጢአት ምርኮ መልሰን ለሕርቃል ድል መንሳትንና በጠላቶቹ ላይ ኃይልን እንደሰጠኸው ለእኛም በኃጢአት ላይ ድል መንሳት መንፈሳዊ ኃይልን ስጠን እያልን እንጾመዋለን፡፡ በጌታ ጾም ላይ እንዲጾም የሆነበት ምክንያት ጾሙ የጌታ ጾም በሚጾምበት ወቅት ላይ ስለተጾመ ቤተክርስቲያናችን አብራ ደንግጋዋለች፡፡እዚህ ላይ በዚያን ጊዜ ለሕርቃል ሕዝቡ ሱባኤ ይዞለታል፡፡ ዛሬም እኛ ለቤተክርስቲያን ያደረግነውን በማሰብ እግዚአብሔር አምላክ ለሕርቃል የሰጠውን በጠላቶቹ ላይ ድል መንሳትን ለእኛም እንዲሰጠን የምንጠይቅበት ስለሆነ የመጀመሪያውን ሳምንት በሕርቃል ሰይመን ጾሙን እንጾማለን፡፡የእኛ ጠላት የጨለማ ገዥ የሆነው ዲያቢሎስ ነውና እሱን ደግሞ በጾም እንደምናሸንፈው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አስተምሮናል፡፡ ጾም ስጋችንን ለነፍሳችን የምናስገዛበት ከፈጣሪ ጋር የምንገናኝበት የጽድቅ መንገድ ለስጋ ጤንነትም ቢሆን አስፈላጊያችን የሆነ አንዱና ዋነኛዉ የጽድቅ እቃ ጦራችን ነዉ፡፡ሆኖም የጾም ወቅት ሲመጣ አቀበት የሚወጡ ይመስል የሚፈሩትና የሚያማርሩት ሳይሆን እንኳን መጣልን ተብሎ  በጉጉት የሚናፈቅ መሆን አለበት፡፡ስለሆነም ማንኛዉም ሰዉ ጾሙን ሲጀምር የሚከተሉትን ጉዳዮች በደንብ ሊያጤናቸዉ ይገባል፡፡

የዲያብሎስን ሥራ ሊያፈርስየተገለጠው የእግዚአብሔር ልጅም በፆም ድል ማድረግን ለእኛ አስተምሮናል። እኛምበዚህ በአብይ ፆም የለመነውና የጠየቅነው ነገር ሁሉ ከኃጢአት በስተቀርእንዲከናወንልን ፆምን ገንዘባችን እናድርግ። በፆም የተጠቀሙ ቅዱሳን አባቶችና ቅዱሳንእናቶች እንዳሉን እናስተውል። በተለይ አሁን በቤተ ክርስቲያን ላይ እየደረሰበሚታየው አስቸጋሪ ፈተና እያንዳንዳችን ልባዊ ፆም በመፆም ልዑል

እግዚአብሔር የፀሎታችንን ምላሽ እንዲሰጠን እንማፀን።

ጾም ጸሎታችን የቅዱሳን አምላክ እግዚአብሔር ይቀበልልን አሜን።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር